Proverbs 22

1መልካም ስም ከብዙ ብልጽግና ይመረጣል፤
መከበርም ከብርና ከወርቅ ይበልጣል።
2ባለጠጋና ድኻ የሚጋሩት ነገር፣
እግዚአብሔር የሁላቸውም ፈጣሪ መሆኑ ነው።

3አስተዋይ ሰው አደጋ ሲያይ መጠጊያ ይሻል፤
ብስለት የጐደለው ግን በዚያው ይቀጥላል፤ መከራም ያገኘዋል።

4ትሕትናና እግዚአብሔርን መፍራት፣
ሀብትን፣ ክብርንና ሕይወትን ያስገኛል።

5በክፉዎች መንገድ ላይ እሾኽና ወጥመድ አለ፤
ነፍሱን የሚጠብቅ ግን ከእነዚህ ይርቃል።

6ልጅን የሚሄድበትን መንገድ አስተምረው፤
ወይም አስጀምረው

በሚሸመግልበት ጊዜ ከዚያ ፈቀቅ አይልም።

7ባለጠጋ ድኻን ይገዛል፤
ተበዳሪም የአበዳሪ ባሪያ ነው።

8ክፋትን የሚዘራ መከራን ያጭዳል፤
የቍጣውም በትር ይጠፋል።

9ቸር ሰው ራሱ ይባረካል፤
ምግቡን ከድኾች ጋር ይካፈላልና።

10ፌዘኛን አስወጣው፤ ጠብ ይወገዳል፤
ጥልና ስድብም ያከትማል።

11የልብ ንጽሕናን ለሚወድድና ንግግሩም ሞገስ ላለው ሰው፣
ንጉሥ ወዳጁ ይሆናል።

12 የእግዚአብሔር ዐይኖች ዕውቀትን ይጠብቃሉ፤
የማይታመኑትን ሰዎች ቃል ግን እርሱ ከንቱ ያደርጋል።

13ሰነፍ፣ “አንበሳ ውጭ አለ፤
መንገድ ላይ እገደላለሁ” ይላል።

14የአመንዝራ ሴት አፍ ጥልቅ ጕድጓድ ነው፤
እግዚአብሔር የተቈጣውም ይገባበታል።

15ሞኝነት በሕፃን ልብ ታስሯል፤
የተግሣጽ በትር ግን ከእርሱ ያርቅለታል።

16ሀብቱን ለማካበት ድኻን የሚበድል፣
ለባለጠጋም ስጦታ የሚያቀርብ፣ ሁለቱም ይደኸያሉ።

የጠቢባን ምክር

17የጠቢባንን ቃል ልብ ብለህ ስማ፤
ልብህም ወደ ትምህርቴ ያዘንብል፤
18በልብህ ስትጠብቃቸው፣
ሁሉም በከንፈሮችህ ላይ የተዘጋጁ ሲሆኑ ደስ ይላልና።
19ስለዚህ እምነትህ በእግዚአብሔር ላይ እንዲሆን፣
ዛሬ አንተን ራስህን አስተምርሃለሁ።
20የምክርና የዕውቀት ቃል የሆኑ፣
መልካም ትምህርቶችን
ወይም ሠላሳ ትምህርቶችን
አልጻፍሁልህምን?
21ለላከህ ተገቢውን መልስ ትሰጥ ዘንድ፣
እውነተኛና የታመኑ ቃሎችን እንዳስተምርህ አይደለምን?
22ድኾች በመሆናቸው ብቻ ድኾችን አትበዝብዛቸው፤
ችግረኛውንም በአደባባይ አታንገላታው፤
23 እግዚአብሔር ይፋረድላቸዋልና፤
የሚቀሟቸውንም ይቀማቸዋል።

24ከግልፍተኛ ጋር ወዳጅ አትሁን፤
በቀላሉ ቱግ ከሚልም ሰው ጋር አትወዳጅ፤
25አለዚያ መንገዱን ትማራለህ፤
ራስህም ትጠመድበታለህ።

26በዋስትና ቃል እጅ አትምታ፤
ለብድር ተያዥ አትሁን፤
27የምትከፍለው ካጣህ፣
የምትተኛበት ዐልጋ ከሥርህ ይወሰድብሃል።

28የቀድሞ አባቶችህ ያስቀመጡትን፣
የጥንቱን የወሰን ምልክት አታፋልስ።

29በሙያው ሥልጡን የሆነውን ሰው አይተሃልን?
በነገሥታት ዘንድ ባለሟል ይሆናል፤
አልባሌ ሰዎችን አያገለግልም።
Copyright information for AmhNASV